ሲከፋው፤
ከተማም እንደ ሰው ልጅ መልክ
የታመቀ ህመም ግርዶሽ
በበሩ ድባብ ይጥላል
የተነከረ ከል ሸማ
የጠቆረ ማቅ ይለብሳል
ፅልመት ፀሐዩን ያደምቃል
ሲቃጠል ብርሃን አይሰጥም
ሲጋይ ሙቀት አይወልድም
እንደ በረዶ ክምር
አጥንት ያቀዘቅዛል
የደም ዝውውር አግዶ
የስትንፋስ ሂደት ይዘጋል
አንድ ባንድ የተካበው ካብ
በቅፅበት ግፊት ተንዶ
በበቀል ክብሪት ይጫራል።
ያልተቀመረ ብሶት ጎርፍ
አይኑን ጨፍኖ ይንዳል
የጊዜን ምልክት ሳያይ
የዘመኑን ስልት ሳያጤን
የመፍትሄ ክር ይበጥሳል።
ሃሳብን ከሰው የማይለይ
በእስትንፋስ የማይፀገይ
ችግኝ ይኮተኩታል።
ከበደች ተክለአብ
እንደ አውሮጳ አቆጣጠር ጁላይ 2020
*ይህ ግጥም ቀደም ሲል በአዲስ አድማስ ጋዜጣ ላይ ለሕትመት በቅቷል።